29/06/2026
ኢመማ 13ኛውን የትምህርት ጥራት ኮንፈረንስ በሀዋሳ ከተማ አካሄደ
የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ከሚያከናውናቸው ትምህርት ነክ ዘርፈ ብዙ ተግባራት መካከል አንዱ የትምህርት ጥራት ኮንፈረንስ ማካሔድ ነው፡፡ በመሆኑም ሀዋሳ ከተማ በሚገኘው የማህበሩ የጋራ ህንፃ ላይ የተለያዩ ተባባሪ አካላት በተገኙበት ሰኔ 18/2018 ዓ/ም 13ኛውን የትምህርት ጥራት ኮንፈረንስ አካሂዷል፡፡
በኢፌደሪ ትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ሚኒስትር ደኤታ ክብርት ወ/ሮ አየለች እሸቴ፣ የሲዳማ ክልል ምክትል ር/መስተዳድር እና የትምህረት ቢሮ ኃላፊ የተከበሩ አቶ በየነ በራሳ፣ የክልሎች፤ ከተማ አስተዳደሮችና የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች መምህራን ማህበር አመራሮች፣ ከሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ፤ትምህርት ኮሌጅ፤ከከተማው በ1ኛ ደረጃ፣ በ2ኛ ደረጃ እንዲሁም ከቴ/ሙያ ኮሌጅ የተውጣጡ መምህራን በኮንፈረንሱ ታድመዋል።
የኢመማ ፕሬዚዳንትና በትምህርት ዓለም አቀፍ አፍሪካን በመወከል የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ አባል ዶ/ር ዮሐንስ በንቲ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉ ሲሆን ማህበሩ ከመምህራን መብትና ጥቅም ጎን ለጎን በትምህርት ሥራ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ ጠቅሰው ይህን ኮንፈረንስ ልዩ የሚያደርገው በማህበሩ ህንጻ የተካሔደ የመጀመሪያው ኮንፈረንስ መሆኑን አመላክተዋል፡፡
የሲዳማ ክልል ምክትል ር/መስተዳድር እና የትምህረት ቢሮ ኃላፊ የተከበሩ አቶ በየነ በራሳም በዚሁ ኮንፍረንስ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ኢመማ ሀገራዊ ኃላፊነቱን እየተወጣ ያለ አንጋፋ ማህበር መሆኑ ብቻም ሳይሆን ሀገራዊ ፋይዳና ትርጉም ያላቸውን ተግባራት በብቃት እየተወጣ ያለ ማህበር በመሆኑ በዚህ ኮንፈረንስ የሚቀርቡ የጥናት ውጤቶች ምክረ ሀሳብን እንደ ክልላችን ወስደን ሥራ ላይ ለማዋል ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡
ክብርት ወ/ሮ አየለች እሸቴ ኮንፈረንሱን በንግግር ከከፈቱት መካከል አንዷ ሲሆኑ ትምህርት ሚኒስቴር ከኢመማ ጋር በትብብር በርካታ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው ተቋርጦ የነበረው የመምህራን የክረምት የሥራ ላይ ከዲፕሎማ ወደ ዲግሪ የትምህርት ደረጃ ማሻሻያ ሥልጠና በያዝነው ክረምት እንደሚጀምር ተናግረው የተለያዩ የመምህራን የጥቅማ ጥቅም ሰነዶችን ከማሀበሩ ጋር እየሰራን ነው በማለት በኮንፍረንሱ የመክፈቻ ንግግራቸው ላይ ተናግረዋል፡፡
ከወለዲያ ዩኒቨርሲቲ፤ከኦሮሚያ ስቴት ዩኒቨርሲተ፤ ከሚዘን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ በግጭት ዙሪያ፣ ቴክኖሎጂን አካቶ ማስተማር ላይ፣ በ12ኛ ክፍል የተማሪ ውጤት ፣በርዕሰ-መምህራን የአመራር ዘይቤ እና በከፍተኛ ትምህርት ጥራት ማረጋገጫ ሥርዓት ላይ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ለውይይት ቀርበው ጥልቅ ውይይት ተደረጎባቸዋል፡፡
በመጨረሻም የጋራ ውይይት ተደርጎ ኮንፈረንሱ በተሳካ ሁኔታ ተጠናቋል፡፡ ይህ ኮንፈረንስ የተሳካ እንዲሆን የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ እና የሀዋሳ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ላደረጉት ድጋፍ ኢመማ በመምህራን ስም ምስጋናውን አቅርቧል፡፡